This blog post is in Amharic, if you are seeing boxes download fonts here.
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 28/2007 (ዋኢማ) – መካካለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ቁጥር መጨመርን ተከትሎ የዜጎችን የምግብ ፍላጎት ለማርካት የእንስሳት ሃብት ምርታማነትን ማረጋገጥ እንደሚያስፈለገ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገለጹ።
ዓለም ዓቀፉ የእንስሳት ሃብት የምርምር ኢንስቲትዩት በኢትዮጵያ 40ኛ ዓመት በዓሉን ዛሬ በአዲስ አበባ አክብሯል።
በዓሉ ”የእንስሳት ሃብት ልማት ለዘላቂ የተመጣጠነ የምግብ ደህንነት፣ ለምጣኔ ሃብት እድገትና ለጤናማ ኑሮ”‘ በሚል ነው የተከበረው።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በበዓሉ ላይ እንዳሉት እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ቁጥር መጨመር ተከትሎ ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት የወተት ፍላጎት በቀጣይ ጥቂት ዓመታት በሶስት እጥፍ ያድጋል፡፡
የሌሎች የእንስሳት ተዋጽኦዎች ፍላጎትም በቀጣይ ጥቂት ዓመታት በከፍተኛ መጠን እንደሚያድግ ይጠበቃል።
በ2050 ዓ.ም ከ9 እስከ 10 ቢሊዮን የሚደርሰውን የህዝብ ቁጥር የምግብ ፍላጎት ለማሟላት የምግብ ምርት በየዓመቱ 70 በመቶ ማደግ እንደሚጠበቅበት ጠቅሰው ይህንን ፍላጎት ለማሟላት አፍሪካ ዘላቂ ምርታማነት ላይ ማተኮር እንዳለባት አስረድተዋል።
ለዚህም የተፈጥሮ ሃብት ይዞታና የአየር ንብረት ለውጥን ባገናዘቡ የግብርና ስልቶች፣ በተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችና በምርት ማሳደግ ላይ የምርምር ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸውና ለዚሁም አመቺ ፖሊሲና አሰራር ሊዘጋጅ እንደሚገባ ነው የተናገሩት።
ግብርናው ለድህነት ቅነሳ፣ ለምጣኔ ሃብት እድገት፣ ለተመጣጠነ ምግብ ደህንነትና ለአካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል።
የእንሰሳት ሃብት ልማቱም ምርት፣ ማቀነባበርና ግብይትን ጨምሮ በተለያዩ የእሴት ሰንሰለቶች ውስጥ ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ዘርፍ መሆኑንም ነው ያስረዱት።
የዓለም አቀፉ የግብርና ልማት ፈንድ ዋና ፕሬዚዳንት ካናዮ ንዋንዜ በእስያና አፍሪካ የመካከለኛው ገቢ ያላቸው ዜጎች ቁጥር መስፋፋት ማሳየቱ የእንሰሳት ተዋጽኦ ምግቦች ፍላጎትን ያሳድገዋል ብለዋል።
በዓለም ላይ 1 ቢሊየን ሰዎች በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ኑሯቸው ከእንስሳት ሃብት ጋር እንደሚዛመድ ገልጸው ሀብቱን በሚገባ በመጠቀም የምግብ ፍላጎትን አነስተኛ አርሶ አደሮችን ማእከል አድርጎ መስራት ያስፈልጋል ነው ያሉት።
”በምግብ አቅርቦት ሰንሰለት ውስጥ የአነስተኛ አርሶ አደሮችን ሚና የምንዘነጋ ከሆነ ድህነትን ማስወገድ አንችልም።” ያሉት ፕሬዚዳንቱ የሴቶች ተጠቃሚነት ሊጎለብት እንደሚገባም ነው ያብራሩት በተለይም በገጠር ያሉ ሴቶች።
”በገጠር አካባቢ ያሉ ሴቶች ምጣኔ ሃብታዊ ተጠቃሚነታቸው ሲረጋገጥ ገንዘቡን ለቤተሰባቸው የኑሮ ደረጃ መሻሻል የማበርከታቸው እድል ከወንዶች ጋር ሲነጻጻር የተሻለ ነው” ብለዋል።
የግብርና ሚኒስትር አቶ ተፈራ ደርበው እያደገ የመጣው መካካለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ቁጥር ማደግ ለዘርፉ መልካም እድል መሆኑን፣ የእንስሳት ሀብት ልማት ከአገሪቱ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት 42 በመቶ ከሚሸፍነው ግብርና ግማሽ ያህሉን ድርሻ እንደሚይይዝ አስረድተዋል።
የምርምር ኢንስቲትዩቱ በእንስሳት አመጋገብ፣ በዝርያ ማሻሻል፣ በእሴት ሰንሰለትና በተለያዩ መስኮች ውጤታማ የምርምር ስራዎችን በኢትዮጵያ ሲያከናውን መቆየቱንም አስረድተዋል።
በተለይም በአቅም ግንባታ ስራዎች ላይ ለተለያዩ የአገሪቱ ባለሙያዎች የአቅም ማሻሻያ ስልጠና ሲሰጥ መቆየቱን በመግለጽ።
አገሪቱ በነደፈችው የአምስት ዓመት የእንስሳት ሃብት ልማት መሪ አቅድ ላይም የጎላ ድርሻ እንደነበረው ጠቁመዋል።
የዓለም አቀፉ የእንስሳት ሃብት የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጂሚ ስሚዝ በአገሪቱ ውስጥ ለነበራቸው የተመቻቸ ሁኔታና የቆይታ ጊዜ መንግስትና ህዝብን አመስግነዋል።
ተቋሙ ለፖሊሲዎች ግብዓት የሚሆኑ ምርምሮችን በተለያዩ መስኮች አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል።
በበዓሉ ላይ በነገው እለት የእንስሳት ሃብትን ከአካባቢ፣ ከዘላቂ የተመጣጠነ ምግብ ዋስትና፣ ከምጣኔ ሃብትና ከጤናማ ኑሮ አንጻር የሚቃኙ ጥናታዊ ጽሁፎች ይቀርባሉ፡፡ (ኢዜአ)
ሌላ የዜና ጥንቅሮች:
- አለምአቀፍ የእንሰሳት ምርምር ኢንስቲትዩት 40ኛ አመቱን በማክበር ላይ ነው
- Livestock production crucial to improve smallholder farmers livelihood
- New livestock master plan for Ethiopia to help secure more revenue from sector
- ኢትዮጵያ ከቁም እንስሳት ሀብት ማግኘት ያለባትን ጥቅም አላገኘችም
- ኢልሪ (ILRI) 40ኛ ዓመቱን እያከበረ ነው: የቁም እንስሳት ዘርፍን ኢኮኖሚያዊ ድርሻ ለማሳደግ እየተሠራ ነው